እንኳን ለአብርሃሙ ሥላሴ ዓመታዊ ክብረ በዓል በሰላም በጤና አደረሰን አደረሳችሁ!

ሐምሌ 7 ቀን እግዚአብሔር አምላክ፣ የአብርሃሙ ሥላሴዎች በአብርሃም ቤት የገቡበትና ሚስቱ ሣራ ይስሐቅን እንደምትወልድ ያበሰሩበት፣ ቸርነታቸውና ፍቅራቸውን የገለጹበት፣ አብርሃምን የባረኩትና መጻዒው ሕይወቱን የነገሩት ዕለት ዕለት ነው፡፡ ዘፍጥረት 18:1-10። ይህ የቅድስት ሥላሴ ክብረ በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ በደማቅ ሥርዓት ይከበራል፡፡

ዛሬም እኛ እንግዶችን በመቀበል፣ ለተራቡ በማብላት፣ ለተቸገሩ በመራራትና በመመጽወት፣ ልቡናችንን ንጹሕ በማድረግና ከኀጢአት በመለየት፣ በደግነት፣ በቀና አስተሳሰብ እና በመሳሰለው ተግባር ከኖርን፤ እግዚአብሔር በሕይወታችን ውስጥ ያድራል፡፡ አድሮም ይባርከናል፤ ይቀድሰናል፡፡ እርሱ ያደረበት ሰውነት ይባረካል፣ ይቀደሳልና፡፡ በጥቅሉ የልባችንን መሻት ዐውቆ የምንሻውን መልካም ነገር ሁሉ ይፈጽምልናል፡፡

የአብርሃምን ቤት የባረኩ ቅድስት ሥላሴዎች የእኛንም ቤት በበረክት ይጎብኙን፣ ህይወታችሁን በተስፋ ይምሉልን!!!