በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንየኦስሎ ማህደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን
  • ቀዳሚ ገጽ
  • ስለ እኛ
  • አገልግሎቶች
    • መርሐ ግብር
    • የህፃናት ጥምቀት
    • የጋብቻ ሥነ-ሥርዓት
    • ፍትሐት
    • ክራዮች
  • የሰንበት ት/ቤት
  • ያግኙን
  • Norwegian
  • Menu Menu

ደመራ እና ብርሃነ መስቀሉ

እንኳን ለደመራ እና ለብርሃነ መስቀሉ በሰላም አደረሳችሁ።

እያልን የደመራን በዓል ዐርብ መስከረም 16 (september 26) ከ 16 ስዓት ጀምሮ በድምቀት እናከበራልን። የበረከቱ ተካፋይ እንድትሆኑ በእግዚአብሔር ስም ጥሪ እናቀርባለን።
አድራሻ – Lille-Wembley, Haugerudveien 79, Oslo

የደመራው ምሥጢር

በሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ

እግዚአብሔር አምላካችን የሠራቸው ታላላቅ ሥራዎች በምልክት የተገለጡ ናቸው፤ ለምሳሌ የሙሴ መስፍንነት፣ የአሮን ሊቀ ካህንነት የተረጋገጠው በአሮን በትር ምልክትነት ነው፡፡ አብርሃም ልጁ ይስሐቅን ሊሠዋ በታዘዘ ጊዜ የሞርያን ተራራ የመረጠው እግዚአብሔር በተራራው ላይ ካሳየው ብርሃን የተነሣ ነው፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምና ቅዱስ መስቀልም የድኅነታችን ምልክቶች ናቸው፡፡ የአሮንና የሙሴ በትሮች፣ የይስሐቅ ቤዛ የሚኾን በግ የተገኘባት ዕፀ ሳቤቅ ደግሞ የእመቤታችንና የመስቀል ምልክቶች ነበሩ፡፡ ወደ ፊት የምንወርሰው መንግሥተ ሰማያት ክርስቶስ ነው፤ እርሱን ደግሞ ያገኘነው ከመስቀል ላይ ነው፡፡

ጥንተ ጠላት ሰይጣን ይህንን ስለሚያውቅ ቅዱስ መስቀሉን አጥብቆ ይቃወመዋል፤ ስለዚህም አይሁድን አነሳሥቶ ከ፫፻ ዓመታት በላይ ተቀብሮ እንዲቆይ አድርጓል፡፡ በመሠረቱ ለሰይጣን ምሥጢሩ ስለማይገባው ነው እንጂ የመስቀሉ ትክክለኛ መቀበሪያ ሥፍራ የምእመናን ልቡና ነው፡፡ ቀራንዮ ለመስቀሉ መትከያነት የተመረጠችውም ቀዳሜ ፍጥረት አዳም የተቀበረው በዚያ ስለ ነበረ ነው፡፡ ቦታው ‹‹የራስ ቅል ሥፍራ›› /ማቴ.፳፯፥፴፪/ መባሉም የኹላችን ራስ አዳም ዓፅሙ በዚያ ስላረፈ ነው፡፡ መስቀሉ በአዳማውያን ፍጥረታት አእምሮ ውስጥ እንጂ ከዚያ ውጪ የሚኖር ባለመኾኑ ተቀብሮ በቆየባቸው ዓመታት ውስጥም ፍቅሩ ከሰው ልጆች ልቡና አልወጣም፡፡

ጠላት በሠራው ተንኮል ተቀብሮ እንዳይቀር መስቀሉን እንድታወጣ መንፈስ ቅዱስ ንግሥት ዕሌኒን አስነሣት፡፡ ይህች ሴት ቤቷ በሀብት፣ በንብረት ሞልቶ በነበረበት ጊዜና በገረድ፣ በደንገጡር በምትንቀሳቀስበት ወቅት ምን እንደ ሠራች አልተመዘገበላትም ነበር፤ ከክብሯ ወርዳ በተጣለችበት ጊዜ ግን እግዚአብሔር ለሚፈልገው ሥራ ምቹ ኾና ተገኘች፡፡ እርሷ በተጣለችበት ባዕድ አገር ውስጥ ኾና የመስቀሉን ነገር ታስብ፤ ብርሃነ መስቀሉም ዘወትር በልቧ ያንጸባርቅ ነበር፡፡ ሐሳቧን እንዲያሳካላት የለመነችው አምላክም ኪራኮስ የተባለውን አይሁዳዊ ሽማግሌ ልኮ አቅጣጫውን አመላከታት፤ ኪራኮስ የጀመረውን ምሥጢርም መልአኩ ‹‹ደመራ ደምረሽ፣ ሰንድሮስ የሚባል ነጭ ዕጣን ጨምረሽ አቃጥዪው›› ብሎ ተረጐመላት፡፡ እርሷም መልአኩ እንደ ነገራት ብታደርግ ጢሱ ሰማይ ደርሶ ወደ ምድር ተመልሶ መስቀሉ ወደሚገኝበት ተራራ ሰገደ፡፡ በጢሱ ምልክትነት መስከረም ፲፯ ቀን የተጀመረው ቍፋሮ መጋቢት ፲ ቀን አልቆ ዕሌኒ መስቀሉን ከልበ ምድር ለማውጣት ችላለች፡፡

መስቀልና ደመራ እንዲህ ነበር የተገናኙት፡፡ ደመራው ለመስቀሉ መገኘት፣ መስቀሉም ለደመራው መሠራት ምክንያት ናቸው፡፡ በዚህ አንጻር መለኮትና ትስብእት በአንድነት መደመራቸው መስቀሉ እንዲሠራ ምክንያት ኾነዋል፡፡ አምላካችን ሥጋ ለብሶ ‹ክርስቶስ› በሚል የተዋሕዶ ስም ሲጠራ ለመከራ መዘጋጀቱን እንረዳለን፡፡ መስቀሉ የሥጋ ብቻ ነበረ፤ አሁን ግን መለኮትም በሥጋ ባሕርይ የመስቀሉ ተካፋይ ኾነ፡፡ ይህም የደመራው ውጤት ነው፡፡ መለኮት አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዘመን መስቀል የተሸከመ ሥጋን ሲዋሐድ መስቀሉን አስወግዶ አልነበረም፡፡ ይኸው በዕፀ በለስ ምክንያት የተሸከምነው መስቀል ነው፡፡ ሥጋ ዓቅም አጥቶ መስቀሉን ከትከሻው ላይ ሳያወርድ ለዘመናት የተጓዘውን ጕዞ መለኮት ኀይል ኾኖት ድካሙን ሳይለቅ ኀያል፤ ኀይሉን ሳይለቅ ደካማ ኾነ፡፡ መስቀል ትርጕሙ መከራ ቢኾነም ነገር ግን እግዚአብሔር ሲያመጣውና ሰው ሲያመጣው ግን ትርጕሙ ይለያያል፤ ሰው ያመጣው መስቀል ኹላችንን ለመከራ፣ ለሞት አሳልፎ ሰጥቶናል፡፡ የእግዚአብሔር መስቀል ግን መከራነቱ ለሰይጣን እንጂ ለእኛ ሕይወታችን ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድም ‹‹መስቀል ብሂል ዕፀ ሕይወት ብሂል፤ መስቀል ማለት የሕይወት ዛፍ ማለት ነው›› በማለት የመስቀልን ትርጕም ነግሮናል፡፡

አዳም ከገነት ሲወጣ በመላእክት እንዲጠበቅ የተደረገው የሕይወት ዛፍ የክርስቶስ መስቀል ነው፡፡ በዕፀ በለስ ምክንያት ኹላችንም እንደ ተጎዳን በዕፀ ሕይወቱም ተጠቃሚዎች ኾነናል፤ አስቀድመን በአዳም መከራ እንደ ተባበርን አሁን ደግሞ በደስታው እንተባበራለን፡፡ ሞትም ሕይወትም አንድ አድርጎናል፡፡ የክርስቶስ መስቀል ኹሉንም በሕይወት አስተባብሯልና፡፡ በአንጻሩ ሰውና ዲያብሎስን ለያይቷል፡፡ የኀጢአት ቁራኝነትን አጥፍቷል፡፡ ጌታችን በማኅፀን ሲፀነስ ጀምሮ የእኛን መስቀል መሸከም ሲጀምር የእርሱ የኾነውን ለእኛ ስለ ሰጠን ከሰይጣን ጋር መለያየታችን በመስቀሉ ተረጋግጧል፡፡ የአምላካችን መስቀል ምልክቱ ደመራ መኾኑ የእኛን ወደ እርሱ መሰብሰብና የጠላታችንን መበተን የሚያረግጥልን ነው፡፡ ጌታችንም ‹‹ወብየ ካልዓትኒ አባግዕ እለ ኢኮና እምዝንቱ ዐፀድ ወኪያሆንሂ ሀለወኒ አምጽኦን ዝየ፤ ከዚህ በረት ያልኾኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱንም ላመጣቸው ይገባኛል›› በማለት ሊሰበስበን እንደ መጣ ነግሮናል /ዮሐ.፲፥፲፮/፡፡ መስቀሉ ፍጥረት አንድ ደመራ ኾኖ የተሠራበት ስለ ኾነ በደመራ እንዲገለጥ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ኾነ፡፡

መስቀሉ አንድ ደመራ ያደረጋቸው ፍጥረታት

፩. ነቢያትና ሐዋርያት

ነቢያት የሚባሉት ከአዳም እስከ ዮሐንስ መጥምቅ ያሉ አባቶች ሲኾኑ፣ ከክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ጀምሮ ለቤተ ክርስቲያን የወንጌልን የምሥራች እንዲነግሩ የተላኩ አባቶች ደግሞ ሐዋርያት ይባላሉ፡፡ በእርግጥ ሐዋርያ የኾነ ነቢይ የለም እንጂ ነቢይ የኾነ ሐዋርያ አለ፡፡ ነቢያትና ሐዋርያት በዘመን፣ በክብር እና በግብር የማይገናኙ ፍጥረታት ናቸው፡፡ መንፈሰ ረድኤት የተሰጣቸው ነቢያት ለሐዋርያት የተሰጠውን መንፈሰ ልደት ለማግኘት አልተቻላቸውም፡፡ ሐዋርያት ግን ኹሉንም አንድ አድርገው ይዘዋል፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ስለዚህ ሲመሰክር ‹‹በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጠን›› በማለት አጕልቶ የተናገረው /ዮሐ.፲፥፲፰/፡፡ ነቢያት በዚህ ምድር የእግዚአብሔርን መንግሥት በመፈለግ ብዙ ደክመዋል፡፡

ሊቃውንቱ ነቢያትን በክረምት፣ ሐዋርያትን በበጋ ገበሬ ይመስሏቸዋል፡፡ የክረምት ገበሬ ላዩ ውሃ፣ ታቹ ውሃ ኾኖበት በጭቃ ወጥቶ በጭቃ ይመለሳል፡፡ ወደ ቤቱ ሲገባም ሚስቱ ጨምቃ ያቆየችለትን ጐመን በልቶ ደስ ሳይለው ይተኛል፡፡ ነቢያትም በዚህ ዓለም በጣዖት አምላኪ ነገሥታት፣ በነቢያተ ሐሰት ስብከት ሲንገላቱ ኖረው ሲሞቱም ሲዖል ይገባሉ እንጂ ገነትን አይወርሱም ነበር፡፡ የበጋ ገበሬ በደረቅ ወጥቶ፣ እሸት በልቶ፣ ተደስቶ ወደ ቤቱ ይመለሳል፤ ከቤቱ ሲገባም እንጀራው በሌማት፣ ጠላው በማቶት፣ ሲቀርብለት ደስ ብሎት ይበላል፤ ይጠጣል፡፡ ሐዋርያትም ልጅነትን አግኝተው ለማስተማር ተልከዋል፤ በሔዱበት ኹሉ ተአምራትን እንዲያደርጉ፣ ልጅነትንም እንዲሰጡ ሥልጣን ተሰጥቷቸዋል፡፡ ሞታቸው ሲደርስም መንግሥተ ሰማያት ተከፍቶ ይጠብቃቸዋል፡፡

ቅዱስ ያሬድም ‹‹ኖትያት ነቢያት ራግናት ሐዋርያት›› በማለት ነቢያትን በዋናተኛ፣ ሐዋርያትን በጀልባ ቀዛፊ መስሎ ይናገራል፡፡ ከቀዛፊዎች ይልቅ ዋናተኞች ይደክማሉ፡፡ ዋናተኞች ውሃው አጥልቋቸው፣ መተንፈስ ተስኗቸው አንዳንዶቹ ከዳር ይደርሳሉ፤ አንዳንዶቹም በድካም በውሃ ውስጥ ሰጥመው ይቀራሉ፡፡ ቀዛፊዎች ግን ምናልባት ሞገድና ማዕበል ካላሰጋቸው በስተቀር ይህ ኹሉ ውጣ ውረድ የለባቸውም፤ በጀልባዋ የተመሰለችው ቤተ ክርስቲያን ለነቢያት በተስፋ እንጂ በአካላ አልተሰጠችም፡፡ ነቢያት ከእርሷ ሳይደርሱ ሞት ቀድሟቸዋል፡፡ ሐዋርያትም በነቢያት ድካም ገብተው ነቢያት የዘሩትን የትንቢት ዘር አጭደዋል፡፡ ወንጌል የነቢያት ዘር ናት፤ ዳሩ ግን ፍሬውን ለመብላት የታደሉት ሐዋርያት ናቸው፡፡ እሸቱ ሲደርስ የገበሬዎቹ የነቢያት ጌታ ክርስቶስ ዘሩን እንዲሰበስቡና እንዲያከማቹ ሐዋርያቱን በእርሻ መካከል ይዟቸው ገብቷል /ማቴ.፲፪፥፩/፡፡ በአበው ፋንታ ውሉድን ለመተካት የመጣው መምህራችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢያትንና ሐዋርያትን በመስቀሉ አንድ ማኅበር አደረጋቸው፡፡ ሐዋርያው መስቀሉን ‹‹ገባሬ ሰላም›› በማለት ይጠራዋል /ኤፌ.፪፥፲፫/፡፡ ነቢያትንና ሐዋርያትን አንድ አድርጎ የእግዚአብሔርን መንግሥት ያወረሰ የክርስቶስ መስቀል ነውና፡፡

፪. ሙታንና ሕያዋን

አዳም በዕፀ በለስ ምክንያት የተሸከመው መስቀል ሞትን አምጥቶብናል፤ ክርስቶስ ስለ ሰው ልጆች ድኅነት ሲል የተሸከመው መስቀል ግን ሞትን ገድሎ ሕይወትን ሰጥቶናል፡፡ በዚህ ምክንያት የሞት መውጊያ ሲሰበር፣ የመቃብር ስቃይ ሲቋረጥ፣ የጨለማ ኀይል ሲሻር ከመስቀሉ ሥር ብዙ ሙታን እንደ አሸን ብቅ ብቅ አሉ፡፡ ምድር እስከዚያች ቀን ድረስ ሙታንን ትቀበል ነበር እንጂ ሕያዋንን ማስገኘት አትችልም ነበር፡፡ ሙታንና ሕያዋን የተፈላለጉበት መስቀል የመጀመሪያው ቀን ነው፡፡ በመስቀል ሙታን ሕያዋንን ፍለጋ ከመቃብር ወጥተው ወደ ከተማ ገቡ፡፡ ከታደለው የሕይወት ስጦታ የተነሣ ሞት አካባቢውን ለቆ ስለጠፋ በሩ እንደ ተከፈተለት እሥረኛ ሙታን ከመቃብር እየወጡ ከተማውን ሞልተውታል፡፡ ይህ ዕለት ሙታንን ከሕያዋን ጋር አፍ ለአፍ ያነጋገረ ዕለት ነው፡፡ ደመራው ሙታንን ከሕያዋን የሚለይ አይደለም፤ ታላቅነቱም እስከ ሲዖል ድረስ የሚታይ ነው፡፡

፫. ጻድቃንና ኀጥአን

የአዳም በደል በሕይወት የሚኖሩ ወንድማማቾችን በሁለት ሐሳብ ከፋፍሏቸው ነበር፡፡ የክርስቶስ የጽድቅ መስቀል ግን አንድ ሐሳብ ፈጠረላቸው፡፡ ጻድቁ አቤል ሳይበድል በደል የደረሰበት፣ ሳይገድል የተገደለ መኾኑ ከክርስቶስ ጋር ቢያመሳስለውም ሞቱ ግን ለሰው ልጆች ድኅነት አልጠቀመም፤ የፍጡር ደም ከእግዚአብሔር ጋር ሊያስታርቀን አይችልምና ኹላችንም በመከራ ውስጥ ለመቆየት ተገደናል፡፡ የክርስቶስ ሞት ግን የድኅነታችን መሠረት ኾነልን፡፡ በቤት ውስጥ የሚዘጋጅ መብራት ከፍ ብሎ ሲቀመጥ ኹሉን እንዲያሳይ ከምድር ከፍ ብሎ የተሰቀለው ክርስቶስም ጻድቃነ ብሊትንና ጻድቃነ ሐዲስን በዓይን እንዲተያዩ አድርጓቸዋል፡፡ በመስቀል ላይ የተፈጸመው ዕርቅ የኀጥአንን በደል ደምስሶላቸዋል፤ የጻድቃንን ጽድቅ አረጋግጦላቸዋል፡፡ ጻድቃንም ኀጥአንም አንድ ኾነው መንግሥቱን በጸጋው ወረሱ፡፡ ኢያሱ በኢያሪኮ እንዳደረገው አሞራውያን ወጥተው እስራኤል ብቻ ምድሪቱን የወረሷት አይደሉም፡፡ መስቀሉ ለኹሉም አንድ መንግሥትን አውርሷቸዋል፤ ጊዜው የደመራ ነውና፡፡ በምድር ደምቆ የታየው ይህ ደመራ እስከ መንግሥተ ሰማያት ድረስም ይቀጥላል፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://lidetalemariam.no/a/wp-content/uploads/Damera_01_adresse-.jpg 3508 2481 webadmin@lidetalemariam.no https://lidetalemariam.no/a/wp-content/uploads/lm-logo.svg webadmin@lidetalemariam.no2025-09-22 17:54:422025-09-22 18:06:36ደመራ እና ብርሃነ መስቀሉ

በፌስቡክ ያግኙን

Search Search

Recent Posts

  • የሀዘን መግለጫና የጸሎት መርሐ-ግብር ጥሪ
  • ፆመ ፅጌ – ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭
  • ደመራ እና ብርሃነ መስቀሉ
  • ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል
  • ጸሎት

Archives

  • February 2026
  • October 2025
  • September 2025
  • July 2025
  • April 2025
  • February 2025
  • January 2025
  • December 2024
  • November 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • July 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • April 2024
  • March 2024
  • February 2024
  • January 2024
  • December 2023
© የኦስሎ ማህደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል Link to: ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል Link to: ፆመ ፅጌ – ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ Link to: ፆመ ፅጌ – ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ ፆመ ፅጌ – ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭
Scroll to top Scroll to top Scroll to top